መዝሙር 32
32
መዝሙር 32
የዳዊት በማስኪል።#32፥0 በሙዚቃ ውስጥ የሚጠቀሙበት ቃል ሳይሆን አይቀርም።
1ብፁዕ ነው፤
መተላለፉ ይቅር የተባለለት፣
ኀጢአቱም የተሸፈነለት፤
2ብፁዕ ነው፤
እግዚአብሔር ኀጢአቱን የማይቈጥርበት፣
በመንፈሱም ሽንገላ የሌለበት፤
3ቀኑን ሙሉ ከመቃተቴ የተነሣ፣
ዝም ባልሁ ጊዜ፣
ዐጥንቶቼ ተበላሹ፤
4በቀንና በሌሊት፣
እጅህ ከብዳብኛለችና፤
ኀይሌም የበጋ ትኵሳት እንደ ላሰው ነገር፣
ከውስጤ ተሟጠጠ። ሴላ
5ኀጢአቴን ለአንተ አስታወቅሁ፤
በደሌንም አልሸሸግሁም፤
ደግሞም “መተላለፌን ለእግዚአብሔር እናዘዛለሁ” አልሁ፤
አንተም የኀጢአቴን በደል፣
ይቅር አልህ። ሴላ
6ስለዚህ የምትታመኑት ሁሉ፣
በጭንቅ ጊዜ ወደ አንተ ይጸልይ፤
ኀይለኛ ጐርፍ አካባቢውን ቢያጥለቀልቅም፣
እርሱ አጠገብ አይደርስም።
7አንተ መሸሸጊያዬ ነህ፤
ከመከራ ትጠብቀኛለህ፤
በድል ዝማሬም ትከብበኛለህ። ሴላ
8አስተምርሃለሁ፤ በምትሄድበትም መንገድ እመራሃለሁ፤
እመክርሃለሁ፤ በዐይኔም እከታተልሃለሁ።
9በልባብና በልጓም ካልተገሩ በቀር፣
ወደ አንተ እንደማይቀርቡት፣
ማስተዋል እንደሌላቸው፣
እንደ ፈረስና እንደ በቅሎ አትሁኑ።
10የክፉዎች ዋይታ ብዙ ነው፤
በእግዚአብሔር የሚታመን ግን፣
ምሕረት ይከብበዋል።
11ጻድቃን ሆይ፤ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ፤ ሐሤትም አድርጉ፤
ቅን ልብ ያላችሁም ሁሉ እልል በሉ።
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.