ትንቢተ ኤርምያስ 24

24
የሁለቱ የበለስ ፍሬ ቅርጫቶች ምሳሌ
1እግዚአብሔር በቤተ መቅደሱ ፊት ለፊት የተቀመጡ ሁለት የበለስ ፍሬ ቅርጫቶችን አሳየኝ፤ ይህም የሆነው የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር የኢዮአቄም ልጅ የሆነውን የይሁዳ ንጉሥ ኢኮንያንን ከይሁዳ መሪዎች፥ ከእጅ ጥበብ ባለሞያዎችና ከሌሎችም ብልኀተኞች ሠራተኞች ጋር ከኢየሩሳሌም ወደ ባቢሎን አስሮ ከወሰደ በኋላ ነው። #2ነገ. 24፥12-16፤ 2ዜ.መ. 36፥10። 2የመጀመሪያው ቅርጫት ከሌሎቹ በፊት ቀደም ብለው የበሰሉ መልካም የበለስ ፍሬዎችን የያዘ ነው፤ ሁለተኛው ቅርጫት ደግሞ ለመብል የማይሆኑ የተበላሹ በለሶችን የያዘ ነው፤ 3እግዚአብሔርም “ኤርምያስ ሆይ! ይህ የምታየው ምንድን ነው?” አለኝ።
እኔም “እነሆ የበለስ ፍሬዎችን አያለሁ፤ ጥሩዎቹ ፍሬዎች እጅግ የተዋቡ ናቸው፤ መጥፎዎቹ ፍሬዎች ደግሞ ለምግብነት ደስ የማይሉና እጅግ የተበላሹ ናቸው” ስል መለስኩለት።
4ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፦ 5“እኔ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ወደ ባቢሎን የላክኋቸውን ሕዝብ እንደነዚህ ጥሩ የበለስ ፍሬዎች እንደ ሆኑ እቈጥራለሁ፤ 6ለሕይወታቸውም በመጠንቀቅ ወደዚህች ምድር እንዲመለሱ አደርጋለሁ፤ አንጻቸዋለሁ፤ አላፈርሳቸውም፤ እተክላቸዋለሁ፤ አልነቅላቸውም፤ 7እኔ እግዚአብሔር መሆኔን እንዲያውቁ አደርጋቸዋለሁ። ከዚያ በኋላም በሙሉ ልባቸው ወደ እኔ ስለሚመለሱ፥ እነርሱ ሕዝቤ ይሆናሉ፤ እኔም አምላካቸው እሆናለሁ።
8“የይሁዳን ንጉሥ ሴዴቅያስንና በዙሪያው ያሉትን አማካሪዎቹን፥ እንዲሁም ከኢየሩሳሌም ነዋሪዎች በዚህች ምድር የተረፉትንና ወደ ግብጽ የወረዱትን ሁሉ ግን ለምግብነት ደስ እንደማያሰኙና እጅግ እንደተበላሹት እንደእነዚያ የበለስ ፍሬዎች አደርጋቸዋለሁ። 9በስደት እንዲበታተኑ ባደረግሁባቸው በምድር መንግሥታት ሁሉ ዘንድ የተጠሉ፥ የተሰደቡ፥ የመነጋገሪያ ርእስ የሆኑ፥ መሳለቂያና የተወገዙ እንዲሆኑ አደርጋቸዋለሁ። 10ለእነርሱና ለቀድሞ አባቶቻቸው ከሰጠኋት ከዚህች ምድር እስኪጠፉ ድረስ በጦርነት፥ በራብና በቸነፈር እንዲያልቁ አደርጋለሁ።”

ማድመቅ

ያጋሩ

ኮፒ

None

ያደመቋቸው ምንባቦች በሁሉም መሣሪያዎችዎ ላይ እንዲቀመጡ ይፈልጋሉ? ይመዝገቡ ወይም ይግቡ