መዝሙር 41
41
መዝሙር 41
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1ብፁዕ ነው፤
ለድኾች የሚያስብ፤ እግዚአብሔር በክፉ ቀን ይታደገዋል።
2 እግዚአብሔር ይጠብቀዋል፤ በሕይወትም ያኖረዋል፤
በምድርም ላይ ይባርከዋል፤
ለጠላቶቹም ምኞት አሳልፎ አይሰጠውም።
3ታምሞ ባለበት ዐልጋ ላይ እግዚአብሔር ይንከባከበዋል፤
በበሽታውም ጊዜ መኝታውን ያነጥፍለታል።
4እኔም፣ “እግዚአብሔር ሆይ፤ ምሕረት አድርግልኝ፤
አንተን በድያለሁና ነፍሴን ፈውሳት” አልሁ።
5ጠላቶቼ በክፋት በመናገር፣ “የሚሞተው መቼ ነው? ስሙስ
የሚደመሰሰው ምን ቀን ነው?” ይላሉ።
6ሊጠይቀኝ የሚመጣ ቢኖር፣
በልቡ ስድብ እያጠራቀመ፣ ከዐንገት በላይ ይናገራል፤
ወጥቶም ወሬ ይነዛል።
7ጠላቶቼ ሁሉ ግንባር ፈጥረው ይንሾካሾኩብኛል፤
እንዲህ እያሉም፣
የከፋ ነገር በላዬ ያውጠነጥናሉ፤
8“ምናምንቴ ነገር ይዞታል፤
ከእንግዲህም ከተኛበት አይነሣም።”
9እንጀራዬን የበላ፣
የምተማመንበትም የቅርብ ወዳጄ፣
ተረከዙን አነሣብኝ።
10 እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ግን ምሕረት አድርግልኝ፤
የእጃቸውን እንድከፍላቸው አስነሣኝ።
11ጠላቴ በላዬ ድል አላገኘምና፣
እንደ ወደድኸኝ በዚህ ዐወቅሁ።
12ስለ ጭንቀቴ ደግፈህ ይዘኸኛል፤
በፊትህም ለዘላለም ታኖረኛለህ።
13የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር፣
ከዘላለም እስከ ዘላለም የተባረከ ይሁን፤
አሜን፤ አሜን።
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.