መዝሙር 112
112
መዝሙር 112
1ሃሌ ሉያ።#112፥1 እግዚአብሔር ይመስገን ማለት ነው።
ብፁዕ ነው፤
እግዚአብሔርን የሚፈራ፣
በትእዛዙም እጅግ ደስ የሚሰኝ፤
2ዘሩ በምድር ላይ ኀያል ይሆናል፤
የቅኖች ትውልድ ትባረካለች።
3ሀብትና ብልጽግና በቤቱ ይሞላል፤
ጽድቁም ለዘላለም ይኖራል።
4ቸር፣ ርኅሩኅና ጻድቅ እንደ መሆኑ፣
ለቅን ሰው በጨለማ ውስጥ ብርሃን ይወጣለታል።
5ለጋስና ያለ ማንገራገር የሚያበድር፣
ሥራውንም በትክክል የሚያከናውን ሰው መልካም ይሆንለታል።
6ለዘላለም ከስፍራው አይናወጥምና፤
ጻድቅ ሰው ሲታወስ ይኖራል።
7ክፉ ወሬ አያሸብረውም፤
ልቡ እግዚአብሔርን በመተማመን የጸና ነው።
8ልቡ የጸና ነው፤ አይፈራምም፤
በመጨረሻም የጠላቶቹን ውድቀት ያያል።
9በልግስና ለድኾች ሰጠ፤
ጽድቁ ለዘላለም ይኖራል፤
ቀንዱም#112፥9 በዚህ ስፍራ ክብርን ያመለክታል። በክብር ከፍ ከፍ ይላል።
10ክፉ ሰው ይህን በማየት ይበሳጫል፤
ጥርሱን ያፋጫል፤ እየመነመነም ይጠፋል፤
የክፉዎችም ምኞት ትጠፋለች።
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.