መዝሙር 116
116
መዝሙር 116
1የልመናዬን ድምፅ ሰምቷልና፣
እግዚአብሔርን ወደድሁት።
2ጆሮውን ወደ እኔ አዘንብሏልና፣
በሕይወት ዘመኔ ሁሉ ወደ እርሱ እጣራለሁ።
3የሞት ወጥመድ ያዘኝ፤
የሲኦልም#116፥3 ዕብራይስጡ መቃብር ይላል። ጣር አገኘኝ፤
ጭንቅና ሐዘን አሸነፈኝ።
4እኔም የእግዚአብሔርን ስም ጠራሁ፤
“እግዚአብሔር ሆይ፤ ነፍሴን ታድናት ዘንድ እለምንሃለሁ” አልሁ።
5 እግዚአብሔር ቸርና ጻድቅ ነው፤
አምላካችን መሓሪ ነው።
6 እግዚአብሔር አላዋቂዎችን ይጠብቃል፤
እጅግ ተቸግሬ ሳለሁ አዳነኝ።
7ነፍሴ ሆይ፤ ወደ ዕረፍትሽ ተመለሺ፤
እግዚአብሔር መልካም አድርጎልሻልና።
8አንተ ነፍሴን ከሞት፣
ዐይኔን ከእንባ፣
እግሮቼን ከመሰናከል አድነሃልና።
9እኔም በሕያዋን ምድር፣
በእግዚአብሔር ፊት እመላለሳለሁ።
10“እጅግ ተጨንቄአለሁ” ባልሁበት ጊዜ እንኳ፣#116፥10 ወይም ያኔ እንኳ
እምነቴን ጠብቄአለሁ።
11ግራ በተጋባሁ ጊዜ፣
“ሰው ሁሉ ሐሰተኛ ነው” አልሁ።
12ስለ ዋለልኝ ውለታ ሁሉ፣
ለእግዚአብሔር ምን ልክፈለው?
13የመዳንን ጽዋ አነሣለሁ፤
የእግዚአብሔርንም ስም እጠራለሁ።
14በሕዝቡ ሁሉ ፊት፣
ስእለቴን ለእግዚአብሔር እፈጽማለሁ።
15የቅዱሳኑ ሞት፣
በእግዚአብሔር ፊት የተከበረ ነው።
16 እግዚአብሔር ሆይ፤ እኔ በእውነት ባሪያህ ነኝ፤
እኔ የሴት ባሪያህ#116፥16 ታማኝ አገልጋይህ ወይም ታማኝ ልጅህ ልጅ፣ ባሪያህ ነኝ፤
ከእስራቴም ፈታኸኝ።
17ለአንተ የምስጋና መሥዋዕት አቀርባለሁ፤
የእግዚአብሔርንም ስም እጠራለሁ።
18በሕዝቡ ሁሉ ፊት፣
ስእለቴን ለእግዚአብሔር እፈጽማለሁ፤
19ኢየሩሳሌም ሆይ፤ ይህን በመካከልሽ፣
በእግዚአብሔር ቤት አደባባይ አደርጋለሁ።
ሃሌ ሉያ።#116፥19 አንዳንዶች እግዚአብሔር ይመስገን ይላሉ።
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.